" ታጣቂዎቹ በየመኪናው የነበሩ ሹፌሮችንና ተሳፋሪዎችን ሳይቀር ነው እየዞሩ የገደሉት " - የአይን እማኝከጎንደር ወደ መተማ በእጀባ ሲሄዱ በነበሩ አሽከርካሪዎች ላይ ከጫካ የወጡ ታጣቂዎች ባደረሱት ጥቃት ከ20 በላይ አሽከርካሪዎች እና ንፁሃን ዜጎች መገደላቸውን የአይን እማኞች ገልጸዋል።
ከትላንትና በስቲያ ሰኞ ሰኔ 16/2017ዓ.ም ከጎንደር ተነስቶ በእጀባ ወደ መተማ ሲጏዙ በነበሩ ብዛት ባላቸው መኪኖች ላይ " መቃ" ተብሎ በሚጠራው ቦታ ላይ ከጫካ የወጡ ታጣቂዎች በፈፀሙት ጥቃት ከ20 በላይ አሽከርካሪዎችና ንፁሃን ዜጎች መገደላቸውን ቲክቫህ ኢትዮጵያ ያነጋገራቸ የአይን እማኞች ገልፀዋል።
ስሙ እንዳይጠቀስ የጠየቀን በቦታው የነበረ አንድ በተለምዶ " አባዱላ " ተብሎ የሚጠራው መኪና አሽከርካሪ ለቲክቫህ ኢትዮጵያ በሰጠው ቃል ፦
" ከጎንደር ወደ መተማ ለመሄድ አጃቢ ስጠብቅ ቆየሁ ከ9:00 በኃላ አንድ አራት ከሚሆኑ ሹፌር ጏደኞቼ ጋር ተነጋግረን እንሄድ በቃ ቀረጥ ከፍለን ብናልፍ ይሻላል ተባብለን ጉዞ ጀመርን።
ከዛ ' መቃ ' የሚባለው ቦታ ላይ ቆመን ለታጣቂዎቹ ቀረጥ ለመክፈል ተራ እየጠበቅን እያለ ከኃላ ሌሎች መኪኖችን ያጀበ አንድ ፓትሮል ሙሉ አድማ ብተና ፖሊስ መጣ ከዛም ታጣቂዎቹ ' መኪኖቹን አስቁሟቸው ቀረጥ ከፍለው ነው የሚያልፉ ' ሲሉ ነገሯቸው ፖሊሶቹም ወርደው ወደ ታጣቂዎቹ ' የታጀበ ተሽከርካሪማ አይከፍልም ' በማለት መልስ ሰጡ። ታጣቂዎቹ መልሰው ' እና ጫካ ያለው ታጣቂ ምን ሊበላልህ ነው ? ' ብለው መለሱ። በዚህ ጭቅጭቅ ተነሳ። በጭቅጭቁ መሀል አንድ ታጣቂ ይመታል ወዲያውኑ ሁኔታው ተቀያየረ።
ከጫቃ በርካታ ቁጥር ያላቸው ታጣቂዎች እየተኮሱ ወጡ ፖሊሶችና ታጣቂዎች ሲጨቃጨቁ ከመኪናቸው ወርደው ጭቅጭቁን ከበው ሲሰሙ የነበሩ አሽከርካሪዎች በሙሉ ተገድለዋል።
በኃላም ታጣቂዎቹ በየመኪናው የነበሩ ሹፌሮችንና ተሳፋሪዎችን ሳይቀር ነው እየዞሩ የገደሉት በአጠቃላይ ከ20 በላይ ሹፌሮችና ንፁሃን ተገድለዋል።
አስከሬናቸውም ትላንት ነው የተነሳው የጎንደር መተማ መንገድ ከትላንት በስቲያ ጀምሮ ተዘግቷል እኔም ትላንት በአብድራፊ ዞሬ ነው ወደ ጎንደር የገባሁት " ብሏል
ጭኑ ላይ በሁለት ጥይት ተመትቶ በመተማ ሆስፒታል እየታከመ ያለ አንድ የአይሱዚ ረዳት መሆኑን ለቲክቫህ ኢትዮጵያ የተናገረው የአይን እማኝ ደግሞ፦
" ወደ መተማ በእጀባ እየተጏዝን እያለን ነበር ተኩሱ የተጀመረው።
እኔና ሹፌሩ መኪና ውስጥ ተቀምጠን እያለ አንድ ታጣቂ መጥቶ ሹፌሩን ገደለና እኔን ሁለት ግዜ ጭኔ ላይ ተኩሶ አቆሰለኝ።
ይህ የሆነው ከ10:30 እስከ 11:00 ሰዓት ነው ታጣቂዎቹ የሚፈልጉትን ከገደሉ በኃላ ሄዱ ብዙ ቆይቶ መከላከያ መጣ የመጣውም ከምሽቱ 2:30 አካባቢ ነበር እኔንም አንስተው ወደ ሆስፒታል የላኩኝ በዚህ ሰዓት ነው።
ከ10:30 እስከ ምሽቱ 2:30 ድረስ ከጏደኛየ አስከሬን ጋር መኪና ውስጥ ነበር የነበርኩት።
ትላንት 18 አስከሬን ተነስቶ ወደ መተማ መጥቷል ከእነዚህ ውስጥ አብዛኛዎቹ የማውቃቸው ሹፌሮች ናቸው " ብሏል።
ሌላው በአንድ ሚኒ ባስ ውስጥ ተሳፍሮ ሲጏዝ የነበረ እና አሁን ቆስሎ መተማ ሆስፒታል የሚገኝ ተሳፋሪ ደግሞ ፦
" ተኩሱ ሲበዛ ወርደን በአንድ የጭነት መኪና ጉማው ስር ተኛን እንደገና ተነስተን እየሮጥን እያለን እግሬ ላይ በጥይት ተመትቼ ወደኩ " ብሏል።
በመተማ ሆስፒታል የሚሰራ አንድ ስሙን መግለፅ ያልፈለገ የህክምና ባለሙያ ትላንት የ3 ሹፌር አስከሬን በሆስፒታሉ ቅጥር ግቢ መመልከቱንና ቆስለው የመጡ ሰዎች በሆስፒታሉ ማከሙን ነግሮናል።
ይህው የህክምና ባለሙያ ቆስለው የገቡ ሰዎች ነግረውኛል ያለውን መረጃ ለቲክቫህ ኢትዮጵያ ሲገልፅ " እርስ በራሳቸው ሲለሚተዋውቁ ሲነጋገሩና ሲደዋወሉ ነበር ከዚህ ተነስተው 21 ሹፌሮች ብቻ ሙተዋል ብለው ነግረውኛል " ብሏል።
የአብዛኛዎቹ ሟቶች አስከሬን ወደ ሆስፒታል አልመጣም ሲልም አክሏል።
ሌላው ተኩስ ከመጀመሩ በፊት በ3 ኬላዎች ላይ 6 ሺ ብር ቀረጥ ከፍሎ ያለፈው ሌላው አሽከርካሪ ሲናገር ምንም እንኳን መንገዱ አለም አቀፍ ቢሆንም ትኩረት ያልተሰጠው ሽፍታ እንደልቡ የሚፈነጭበት መንገድ ነው ይላል።
" በዚህ መስመር በሆና ፣ ግንትና መቃ በሚባሉ ቦታዎች ላይ 3 ኬላዎች አሉ እንደ ህጋዊ ተቆጥረው ነው ገንዘብ የሚሰበስቡት ሁለት አመትም እየተጠጋቸው ነው " ብሏል።
" ' መቃ ' ላይ ታጣቂዎች ምንም ነገር የሚፈሩ አይደሉም እንዴት የመንግሥት ፀጥታ ኃይል አጅቦ የሚያልፍን ተሽከርካሪ ቀረጥ ክፈል ይላሉ ከዛም አልፈው ይከራከራሉ ፤ ፀጥታ ኃይል ላይም ይተኩሳሉ ? ሽፍታ ይሄን ያህል ድፍረት ከየት አመጣ ከጀርባቸውስ እነማን ቢኖሩ ነው ? " ሲል ጠይቋል።
በጥቃቱ ዙሪያ እስካሁን ከመንግስትም ሆነ ከሌላ ሶስተኛ ወገን የተባለ ነገር የለም።
ቲክቫህ ኢትዮጵያ
ባህር ዳር
#TikvahEthiopiaFamilyBD
@tikvahethiopia