ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ መንፈሳዊነትና ፖለቲካን ለይተን መጎዝ ይኖርብናል ሲሉ ጥሪ አቀረቡ !
ግንቦት 25 ቀን 2017 ዓ.ም (ተ.ሚ.ማ/አዲስ አበባ)
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሀይማኖት በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በተመረጡት ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጅና ብፁዕ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ የአቀባበል መርሐ ግብር ላይ ተገኝተው ባስተላለፉት አባታዊ መልዕክት የእግዚአብሔር ቤት በእግዚአብሔር መንገድ ብቻ መመራት ይኖርበታል ብለዋል።
የእግዚአብሔር ቤት በአምልኮተ እግዚአብሔርና በጸሎት ከመራነው ሁሉም ነገር ቀና ይሆናል ዓለማዊ መንገድ ከተደባለቀበት ግን አደገኛ ነው "ጋሻና ቅል ለየቅሉ ይሰለል።" እንደሚባለው መንፈሳዊነትና ፖለቲካን ለይተን መጎዝ ይኖርብናል ብለዋል።
አያይዘውም ለአዲሶቹ አመራሮች የሁላችንም ድጋፍና ጸሎት ያስፈልጋቸዋል፤ ስለሆነም ሁላችንም እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ እንደ አንድ ልብ መካሪ በመሆን በሀቅና በቅንነት ልናግዛቸው ይገባል ብለዋል።
ይህችን ታላቅ ቤተክርስቲያን በእግዚአብሔራዊ መንገድ ሰርተን ካልጠበቅናት አደጋው የከፋ ይሆናል። ያሉት ቅዱስነታቸው ይህን በመገንዘብም ቤተክርስቲያናችንን በቀና መንገድና በመንፈሳዊነት መምራት ይኖርብናል ብለዋል።
ሰላም የሚገኘው ከሰላማዊቷ ቤተክርስቲያን ነው ያሉት ብፁዕ ወቅዱስ አበነ ማትያስ ከቤተክርስቲያን ያልተገኘ ሰላም ከየት ሊገኝ ይችላል? የተሰጠን ኃላፊነት መንፈሳዊ መሆኑን ግንዛቤ ውስጥ በማስገባትም ለሀገራችን ሰላም የበኩላችንን አስተዋጽኦ ለማበርከት በትጋት መስራት ይኖርብናል ብለዋል።
ጥላቻ፣ዘረኝነት፣ጎጠኝነት አይጠቅምም እኛ መንፈሳዊያን ነን እግዚአብሔር ሲፈጥረን ንፁሃን አድርጎ ነው የፈጠረን እኛ በራሳችን መንገድ በመጓችን ነው ወርደን ተጠባቂዎች የሆነው፤
ያሉት ቅዱስነታቸው እኛ ጠባቂዎች መሆናችንን አውቀን የጠባቂነት ሚናችንን ከጥላቻና ከዘረኝነት በራቀ መንገድ በመፈጸም ለሰይጣን ሳይሆን ለእግዚአብሔር ተመችተን መገኘት አለብን ነው ያሉት።
በመጨረሻም አሁን ለተመረጡት አባቶች እግዚአብሔር አምላክ ጽናትንና ብርታትን ይስጥልን፤ የአገልግሎት ጊዜአቸውን ጨርሰው የተሰናበቱትን አባቶችም እግዚአብሔር አምላክ በቸርነቱ ይጠብቅልን ሥራዎቻቸውን ሁሉ ይባርክ በማለት መርሐ ግብሩን በጸሎት አጠናቀዋል።
╭══•|❀:✧๑♡๑✧❀|: ══╮
@News_Tewahdo╰══•ೋ•✧๑♡๑✧• ══