እስራኤል እና ኢራን ትላንት ምሽት በዶናልድ ትራምፕ አማካኝነት የተኩስ አቁም ስምምነት ላይ መድረሳቸው ቢነገርም ፣ ዛሬ ረፋድ ላይ ኢራን በእስራኤል ላይ ሚሳኤል ማስወንጨፏን ተከትሎ ስምምነቱ መፍረሱን የእስራኤል መከላከያ ሚኒስቴር ገልጿል፡፡
አስራ ሁለተኛ ቀኑን በያዘው የእስራኤል ኢራን ጦርነት በመካከለኛው ምስራቅ አንጃቦ የነበረውን የቀውስ አዙሪት በዚሁ የሰላም ስምምነት መፍትሄ ይበጅለታል ተብሎ ቢገመትም ዛሬ መጣሱ ግን ቀጠናውን ለሌላ ውድመትና እልቂት እንዳይዳርግ እየተሰጋ ነው፡፡
ከትላንት ወዲያ አሜሪካ በኢራን ሶስት ቁልፍ የኒውክለር መሰረተ ልማቶች ላይ የቦምብ ድብደባ ማድረጓን ተከትሎ ኢራንም አጸፋዊ እርምጃዬ ነው ባለው ጥቃት ኳታርና ኢራቅ የሚገኘውን የአሜሪካ የጦር ሰፈር ደብድቢያለሁ ብላለች፡፡
ከአሜሪካ የቦምብ ድብደባ በኋላም ኢራን የሆርሙዝ ሰርጥን እንድትዘጋ የሀገሪቱ ፓርላማ መወሰኑ የሚታወስ ሲሆን ይህ ውሳኔ እንዲተገበር ደግሞ የኢራን ጠቅላይ ብሔራዊ የደህንነት ምክር ቤትን ይሁንታ እስከዛሬ ድረስ እየጠበቀ ይገኛል፡፡
የሆርሙዝ የባህር ሰርጥ የተለያዩ የነዳጅ ምርቶችን የጫኑ መርከቦች በዋነኝነት የሚተላለፉበት ሲሆን የዓለም አንድ አምስተኛው ወይም ከ20 በመቶ በላይ የነዳጅ ፍጆታ በዚሁ ሰርጥ በኩል ነው የሚሳለጠው፡፡
በየቀኑ ብቻ 20.3 ሚሊዮን በርሜል የነዳጅ ምርት ይተላለፍበታል የሚባለው የሆርሙዝ ባህር ሰርጥ ቢዘጋ ኢትዮጵያን ጨምሮ ህንድ፣ ቻይና፣ ጃፓን፣ ደቡብ ኮሪያና የአውሮፓ ህብረት አባል ሀገራት የገፈቱ ቀማሽ ይሆናሉ፡፡
እንደ ኢትዮጵያ ያሉ የነዳጅ ምርቶችን በከፍተኛ ወጭ የሚያስገቡ ሀገራት በዚሁ የመካከለኛው ምስራቅ ግጭት የተነሳ በአንድም ይሁን በሌላ መልኩ የዋጋ ንረቱ በቀጥታ ተጽዕኖ ሊያሳድርባቸው ይችላል፡፡
እንዴት የሚለውን ደግሞ እንመልከት!ዘ ኦቭዘርቫቶሪ ኦፍ ኢኮኖሚክ ኮምፕሌክስ የተባለና ዓለም አቀፋዊ የንግድና ኢኮኖሚያዊ መረጃዎችን በማቅረብ የሚታወቀው የበይነ መረብ የመረጃ ማዕከል ይዞት የወጣው መረጃ እንደሚያመላክተው ኢትዮጵያ በፈረንጆቹ 2023 ብቻ 2.5 ቢሊዮን ዶላር አውጥታ ድፍድፍ ነዳጅ በመግዛት ከዓለም 72ኛ ደረጃ ላይ አስቀምጧታል፡፡
እንደመረጃው ከሆነ ኢትዮጵያ በፈረንጆቹ 2022 እና 2023 ድፍድፍ ነዳጅ ከገዛቻቸው ሀገራት መካከል የገልፍ ሀገራት ቀዳሚ ሲሆኑ፣ ኩዌት ደግሞ ለኢትዮጵያ ከፍተኛ ነዳጅ አቅራቢ በመሆን ቅድሚያውን ትይዛለች ፤ ከኩዌት በማስከተልም ሳዑዲ አረቢያና የተባበሩት አረብ ኤሚሬቶች ይከተላሉ፡፡
ታዲያ እነዚህ ነዳጅ ሻጭ ሀገራት ምርታቸውን ለማጓጓዝ አብዛኛውን የሆርሙዝ ባህረ ሰርጥን የሚጠቀሙ እንደመሆናቸው ይሄው መተላለፊያ ከተዘጋ የነዳጅ ዋጋ ከ13 በመቶ በላይ ሊጨምር እንደሚችል ነው ትንበያዎች የሚያመለክቱት፡፡
ከትላንት ወዲያ ንጋት አሜሪካ የኢራን ኒውክሌር ማብላያዎችን በቦምብ ከደበደበች በኋላ እንኳን የነዳጅ ዋጋ ላይ ወደ 1.4 በመቶ ገደማ ጭማሪ መስተዋሉን አለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል፡፡
ኢትዮጵያም በነዳጅ ግብይት በኩል የሆርሙዝ ሰርጥን ከሚጠቀሙ ሀገራት ጋር ቀጥተኛ የንግድ ትስስር ያላት እንደመሆኑ የመካከለኛው ምስራቅ ሀገራት ቀውስ ጫናው አይቀሬ ያደርገዋል፡፡
የኢቢኤስ አዲስ ነገር ዲጂታል ዴስክ ይሄንኑ ጉዳይ በተመለከተ ለነዳጅ አቅራቢዎች ድርጅት እንዲሁም ለንግድና ቀጠናዊ ትሥሥር ሚኒስትር የሆርሙዝ ሰርጥ ቢዘጋ በኢትዮጵያ ላይ የሚያሳድረው ተጽዕኖ ይኖረው ይሆን?! የሚለውን ለመጠየቅ ያደረግነው ተደጋጋሚ የስልክ ሙከራ አልተሳካም፡፡
#EBS
#EBSTVNEWS
#EBSTVSPORT
#_7696_WN
https://t.me/ebstvnews