ተቋማቱ በመቀናጀት ጊዜን የቀደሙ ሥራዎች መስራት አለባቸው - የሁለቱ ተቋማት የሥራ ኃላፊዎች
አስተማማኝና ተደራሽ የኃይል አቅርቦት እንዲኖር የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይልና የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ተናበው ጊዜን የቀደሙ ሥራዎችን ማከናወን እንዳለባቸው የሁለቱ ተቋማት የሥራ ኃላፊዎች ገለጹ።
በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የኤሌክትሪክ መሠረተ ልማት ማናጅመንት ሥራ አስፈፃሚ ዶ/ር ገበየሁ ሊካሳ እንደገለፁት ሁለቱ ተቋማት እስከ 2006 ዓ.ም ድረስ በአንድ ተቋም ሥር የኃይል አቅርቦቱን ተደራሽ ለማድረግ በርካታ ሥራዎችን ሲያከናውኑ ቆይተዋል፡፡
የኃይል ፍላጎት እያደገ በመምጣቱ እና ዘርፉ ለሀገር ሁለንተናዊ ዕድገት ወሳኝ መሆኑን በመረዳት ዓለምአቀፋዊ ተሞክሮዎችን በመገምገም አቅርቦቱንና ተደራሽነቱን ለማሳደግ ሲባል በጥናት ላይ በመመስረት ሁለቱ ተቋማት ራሳቸውን ችለው እንዲደራጁ መደረጋቸውን ተናግረዋል።
የተቋማቱ ወደ ሁለት መከፈል ትኩረት እንዳይበታተን በማድረግ እንዲሁም የፋይናንስ ጫናዎችን በማቃለል አቅርቦቱን ከማዘመን እና ተደራሽነቱን ከማስፋት አንጻር አበረታች ውጤት እንዲመዘገብ ማስቻሉን ጠቁመዋል።
ዶ/ር ገበየሁ አክለውም የውስጥ አሰራርን በማዘመን የነባር ኔትወርኮችን መልሶ ግንባታ እና የአቅም ማሳደግ ሥራዎችን በማከናወን የኃይል መቆራረጡን በመቀነስ ተደራሽነቱን ማሳደግ ተችሏል ብለዋል።
በዚህም ባለፉት 11 ዓመታት ተቋማቱ ባከናወኗቸው ሥራዎች የደንበኞችን ቁጥር ከ1 ነጥብ 2 ሚሊዮን ወደ 5 ነጥብ 2 ሚሊዮን እንዲሁም የተደራሽነት ሽፋኑን ከ30 በመቶ ወደ 54 በመቶ ከፍ ማድረግ መቻሉን ገልፀዋል፡፡
ተቋማቱ በአደረጃጀት ለሁለት ቢከፈሉም ሥራቸው ተመጋጋቢ እና ኔትወርኩም የተያያዘ በመሆኑ እያደገ የመጣውን የኃይል ፍላጎት ለመመለስና ተደራሽነቱን ለማሳደግ የጋራ የግንኙነት ጊዜ አስቀምጠው እየሰሩ መሆኑን ገልፀዋል።
የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል የኮርፖሬት ኮሙኒኬሽን መምሪያ ዳይሬክተር አቶ ሞገስ መኮንን በበኩላቸው 78 ከመቶ ከግሪድ እንዲሁም 22 ከመቶ ከግሪድ ውጭ የኃይል አቅርቦቱን ተደራሽ ለማድረግ የተያዘውን ሀገራዊ ዕቅድ ለማሳካት ሁለቱ ተቋማት ተናበው መስራት እንዳለባቸው አብራርተዋል፡፡
የኃይል ተደራሽነቱን ከማሳደግ በተጨማሪ ቀደም ሲል የኃይል ተጠቃሚ የነበሩ አካባቢዎች የኃይል ፍላጎት በከፍተኛ ደረጃ እያደገ መሆኑንና ይሄን ጥያቄ ለመመለስ ሁለቱ ተቋማት ተናበው ጊዜን የቀደሙ ሥራዎች መስራት አለባቸው ብለዋል፡፡
እንደ ዳይሬክተሩ ገለፃ መናበቡን መዋቅራዊ አድርጎ ለመቀጠል በሁለቱ ተቋማት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች የሚመራና ሥራዎችን የሚገመግም ቡድን ተዋቅሮ እየተሰራ ነው።
ወቅታዊና ትክክለኛ መረጃችን ለማግኘት ይፋዊ የማኅበራዊ ትስስር ገጾችን ይቀላቀሉ!
[Facebook]
http://www.facebook.com/EEUOfficial[Telegram]
https://t.me/eeuethiopia[Website]
http://www.eeu.gov.et[YouTube]
https://www.youtube.com/@EthiopianElectricUtility[Tiwtter]
https://x.com/EEUEthiopia [TikTok]
https://www.tiktok.com/@ethiopian.electri [Whatsapp]
https://www.whatsapp.com/channel/0029VbAAvBDE50UZXJlIl507