በወሎ አካባቢዎች የተማሪዎች እና መምህራን ስደት በከፍተኛ መጠን ጨመረ ተባለ‼️
በሰሜን ወሎ፣ ደቡብ ወሎ እና ኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞኖች የተማሪዎች እና የመምህራን ስደት እየጨመረ ነው። በአንዳንድ ወረዳዎች ወላጆች ልጆቻቸውን እስከ ስምንተኛ ክፍል ድረስ ብቻ በማስተማር ወደ አረብ ሀገራት ይልካሉ። በ2017 ከሐብሩ ወረዳ ብቻ ወደ 52 መምህራን ሥራ መልቀቃቸውን የአካባቢው ባለሥልጣናት ተናግረዋል።
ትምህርታቸውን እያቋረጡ ወደ አረብ አገር በስደት ከሚሄዱ ተማሪዎች በተጨማሪ መምህራን የስደቱ አንድ አካል መሆናቸውን የባቲ እና ተሁለደሬ ወረዳ የትምህርት ባለሙያዎች ይናገራሉ፡፡
‹‹መምህራን ራሱ የስደቱ አንድ ሰለባ ሆነዋል፡፡ ከመምህራንም ግማሹ በህጋዊ መንገድ በህገወጥ መንገድም የሚሄዱ አሉ፡፡ ከአንድ ትምህርት ቤት ምሳሌ ለማንሳት ሰባት(7) መምህራን ለቀዋል፡፡
ባቲ ወረዳ ኤላ ትምህርት ቤት፡፡››
በተመሳሳይም በሰሜን ወሎ ሀብሩ ወረዳ የህገወጥ የሰዎች ዝውውር ኮሪደር በመሆኑ በአካባቢው የሚገኙ ተማሪዎች ትምህርት አቋርጠው ስደትን ምርጫ ቢያደርጉም የመምህራን ስራ አቋርጦ መጓዝ ግን አስደንጋጭ መሆኑን የወረዳው የሀብሩ ወረዳ ትም/ት ጽ/ቤት ሃላፊ አቶ መንግስቱ ደረጀ ይናገራሉ፡፡
‹‹የማቋረጥ ምጣኔው የተማሪዎች ብቻ ሳይሆን መምህራን በዘንድሮው አመት ላይ ወደ 52 መምህራን ለቀዋል፡፡ ግማሹ አረብ ሀገር የሄደ አለ፤ ግማሹ ሌላ ስራ ይዟል፤ የሚሄዱት ግን ተማሪዎች ፍልሰት ባለበት ህገወጥ የሰዎች ዝውውር በሚከወንበት አካባቢ ያሉት ናቸው፡፡››
በስደት ወደአረብ ሀገር በሚደረግ ጉዞ ምክንያት የትምህርት ዘርፉ ችግር እያጋጠመው ነው የሚሉት የደቡብ ወሎ ዞን ትምህርት መመሪያ ሃላፊ አቶ አለምነው አበራ ማህበረሰቡ ለስደት ያለው የተሳሳተ አመለካከት ፈተና ሆኗል ይላሉ፡፡
‹‹ አሁን ተሁለደሬ ወረዳ በረሃ ውስጥ አንድ ትም/ቤት አለ እነርሱ ልጆቻቸውን የሚያስተምሩት እስከ 8ኛ ክፍል ብቻ ነው፡፡
የ8ኛ ክፍል መልቀቂያን ካርድ እስከሚይዙ ማለት ነው፡፡ ከዚያ በኋላ ልጆቻቸውን ወደ አረብ ሀገር ልከው የማን ነው ልጅ ብር ይዞ የመጣ ነው እንጂ ማን አስተምሮ ዶ/ር አደረገ የሚል የለም፡፡ እና በጣም የከፋ ነው፡፡ ሽፋኑን ስናየው ደግሞ በየአመቱ የ2ኛ ደረጃ እየቀነሰ ነው"ብለዋል።
(Dw)
@ethio_mereja_news@ethio_mereja_news